ኢትዮጵያን ጨምሮ 4ቱ ሀገራት የጤና እቅዳቸውን የሚያሳኩበትን ሚሊዮኖችን አገኙ
የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ በኢትዮጵያና በሌሎች የሰሃራ በታች አፍሪካ ሀገራት የጤና እቅዶችን ለማገዝ የ10 ሚሊዮን ዩሮ ድጋፍ አደረገ
የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ (EIB) የልማት ዘርፍ የሆነው ኢአይቢ ግሎባል (EIB Global)፣ የሰሃራ በታች የአፍሪካ ሀገራት ሰፊ የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ፋይናንስ ሊስቡ የሚችሉ ሀገራዊ የጤና ፕሮጀክቶችን እንዲቀይሱ ለመርዳት የ10 ሚሊዮን ዩሮ የቴክኒክ ድጋፍ ፕሮግራም ይፋ ማድረጉን ካፒታል ዘግቧል።
በዚህ አዲስ ፕሮግራም መጀመሪያ ላይ ከተካተቱት አራት የአፍሪካ ሀገራት መካከል አንጎላ፣ ቡሩንዲ፣ ኢትዮጵያ እና ዛምቢያ ይገኙበታል። ይህ የቴክኒክ እገዛ በዋናነት የመሠረታዊ ጤና እንክብካቤ ኢንቨስትመንትን ለማፋጠንና የፕሮጀክቶችን እቅድ፣ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ጉዳዮች እንዲሁም አወቃቀራቸውን በማጠናከር ሁሉን አቀፍ የጤና ሽፋን ተደራሽነትን ለማሳደግ ያለመ ነው።
ይህ ድጋፍ እየቀረበ ያለው በኢአይቢ ግሎባል ፣ በእስልምና ልማት ባንክ እና በዓለም ጤና ድርጅት በጋራ በተመሰረተው "የጤና ተፅዕኖ ኢንቨስትመንት መድረክ" (HIIP) አማካኝነት ነው። ሶስቱ ተቋማት ለቴክኒክ እገዛ እና ለአቅም ግንባታ የሚሆን የ30 ሚሊዮን ዩሮ መነሻ ፈንድ ያዋጡ ሲሆን፣ ለጤና ፕሮጀክቶች ተጨማሪ የገንዘብ ድጋፍ ለመሳብም አቅደዋል።
የባንኩ ምክትል ፕሬዝዳንት ማሬክ ሞራ እንደገለጹት፣ ይህ ከዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር የተደረገው ጥምረት የመንግስት እና የግል ባለሀብቶች በጋራ ሲሰሩ የሚያመጡትን ውጤት የሚያሳይ ሲሆን፣ ይህም ስጋቶችን ለመቀነስ፣ የግል ካፒታልን ለማሳተፍ እና ኢንቨስትመንቶችን ከሀገር በቀል ፍላጎቶችና ከዓለም አቀፍ የጤና ፖሊሲዎች ጋር ለማጣጣም ትልቅ እገዛ ያደርጋል።
What's Your Reaction?